Accessibility links

Breaking News

የምድር ቀን


በያመቱ በሚያዝያ ወር የሚከበረው የምድር ቀን ተፈጥሮን እና አካባቢያችን ከማክበርም በላይ ነው። ለተፈጥሮ እና አካባቢ ጥበቃ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች መነቃቃት ስፍራ ይሰጣል።

“እአአ በ1970 የመጀመሪያው የምድር ቀን በተከበረበት ወቅት፣ የአየር እና የውሃ ጥራትን ለመጠበቅ፤ ከምድር ለመጥፋት የተቃረቡ የእንስሳት ዝርያዎችን ለማዳን እና እንዲሁም የዩናይትድ ስቴትስ የአካባቢ ጥበቃ ድርጅትን ለማቋቋም የወጡ ህጎችን ሥራ ላይ በማዋል ተፈጽሟል” ሲል በአየር ንብረት ላይ የተደቀኑ ፈተናዎችን ለመቋቋም አዲስ እና ጠንካራ እርምጃዎች በሚል የሰፈረው የዕለቱ ርዕሰ አንቀጽ ይንደረደራል።

ይህም የተፈጥሮ አካባቢ መራቆት የሚያስከትላቸውን ችግሮች ለመቅረፍ የተወሰዱ ተከታታይ ሁነኛ እርምጃዎች አካል እንደነበር በማስታወስ በያዝነው ዓመት በመሬት ቀን እና ከዚያ ቀደም ብለው በነበሩ ሳምንታት የባይደን-ሃሪስ አስተዳደር በዓለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ቀውስን ለመቋቋም የተነደፉ አዳዲስ ፖሊሲዎችን ያካተተ ሌላ ግዙፍ እርምጃ ማስተዋወቁን አመልክቷል።

ርዕሰ አንቀጹ አያይዞም፣ “ይህም በአገር ውስጥ እና በዓለም ዙሪያ የደን ጭፍጨፋን ለመዋጋት፣ ሁለት አዳዲስ ለባህር እንስሣት እና ዕጽዋት ጥበቃ የሚያገለግሉ ምቹ ሥፍራዎችን በመፍጠር የውቅያኖሱን የተፈጥሮ ይዞታ በማረጋገጥ፣ የዓሣ ዝርያዎችን ጫርሶ እንዳይጠፉ ለማድረግ የሚወስዱ የጥንቃቄ እርምጃዎችን፣ በባህር ማጓጓዣው ዘርፍ የካርቦን ብክለትን የሚያስከትሉ ሁኔታዎችን መቀልበስ እና የፕላስቲክ ምርቶች የሚያመጡትን ጉዳት ለመቋቋም፣ እንዲሁም የባህር ዳርቻ ታዳሽ ኃይል ምንጮችን ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችሉ ተከታታይ ውጥኖችን እና ያለንን ቁርጠኝነት ይጨምራል፤” ብሏል።

እነዚህ ውጥኖች በባይደን-ሃሪስ አስተዳደር የመጀመሪያዎቹ 14 ወራት ውስጥ በተከናወኑት ረጅም ዝርዝር ያዘሉ እርምጃዎች ላይ የሚታከሉ” መሆናቸውን፣ የዩኤስ-ቻይና የጋራ የግላስጎው ሥምምነት በመባል የሚታወቀውን በ2020ዎቹ ወሳኝ አስርት ዓመታት ውስጥ የአየር ንብረት ጥበቃን ለማረጋገጥ የሚወሰዱ እርምጃዎችን ለማፋጠን እና ለአደጋ ተጋላጭ የሆኑ አገሮችን የአየር ንብረት ለውጥ የሚያደርስባቸውን ጉዳት መቋቋም የሚያስችል አቅም ለመገንባት በትብብር የሚሰራውን ሥራ እና እንዲሁም የአየር ንብረት ቀውሱን ለመታደግና ሳይንሱ ግድ የሚላቸውንም ለማሟላት፣ መላውን ዓለም ለማነሳሳትና ለማስተባበር በሚደረገው ጥረት ከ40 የዓለም መሪዎች ጋር በርቀት በቪዲዮ አማካኝነት የሚካሄድ የአየር ንብረት ጉባኤ መጥራት ዕቅድም ይዟል።” ሲል ያስረዳል።

ርዕሰ አንቀጹ በተጨማሪም "ይህ የባይደን-አስተዳደር የግሪንሃውስ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ ዓለም ያለውን መነሳሳት በማጎልበት፣ በአየር ንብረት ለውጥ ያተኮሩ ዕቅዶቻችንን የሰፊው ፖሊሲያችን አካል

በማድረግ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ለሚያግዙ ሥራዎች የምናውለውን መዋዕለ ንዋይ በከፍተኛ መጠን በማሳደግ የአየር ንብረት ቀውስን መዋጋት ቅድሚያ የሚሰጠው የውጪ ፖሊሲ ተግባራዊ አድርጓል።

ዩናይትድ ስቴትስ ለተጫወተችው የመሪነት ቁልፍ ሚና ምስጋና ይድረስና በእንግሊዝኛው ምህጻር /COP26/ በመባል በሚታወቀው የግላስኮው ሥምምነት ዓለም የከባቢ ዓየር ግለት መጠን ከ1 ነጥብ 5 ዲግሪ ሴልሺየስ በላይ እንዳይጨምር ለማድረግ ከተያዘው ገደብ ለመድረስ በእጅጉ ተቃርቧል” ሲሉ የዩናይትድ ስቴትሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንተኒ ብሊንከን የዓመቱን የምድር ቀን አስታከው የታናገሩትን አስታወሷል።

በተጨማሪ “ኔት ዜሮ ኢኮኖሚ” በመባል የሚታወቀውን እና ወደ ከባቢ ዓየር የሚለቀቀው በኣንድ ወገን ከከባቢ ዓየር የሚገፈው የበካይ ጋስ መጠን እኩል እንዲሆን እና ተጨማሪ ብክለት እንዳይኖር የሚያስችል የምጣኔ ሃብት አቅጣጫ ለመከተል እንደ አውሮፓውያን የዘመን አቆጣጠር ለ2050 ዓም በተያዘው የፓሪሱ ስምምነት መሰረት ዩናይትድ ስቴትስ የነደፈችውን የረጅም ጊዜ ዕቅድ ይፋ አድርገናል፤ እንዲሁም ከአውሮፓ ህብረት ጋር በመሆን የዓለማችንን የዓየር ግለት መጨመርን ለመገደብ ከአጭር ጊዜ ግብ አንጻር እንደ ብቸኛው እጅግ ውጤታማ ዕቅድ ተደርጎ የሚታየውን የከባቢ ዓየር በካይ የሆነውን የሚቴን ጋስ ልቀት ለመቀነስ በሚደረገው ትግል የሚሳተፉ ከአንድ መቶ በላይ አገሮች አስተባብረናል።

ያለፈውን ዓመት መለስ ብለን ስናስተውል፣ ጤናማ ፕላኔት ጠብቆ ለማቆየት በዓለም አቀፍ ደረጃ በገባነው የቁርጠኝነት ቃል መሰረት አንዳች ግስጋሴ እንደተመዘገበበት

ዓመት ለማሰብ ችለናል" ሲሉ ብሊንከን የተናገሩትን ጠቅሶ የዕለቱ ርዕሰ አንቀጽ ሃተታውን ደምድሟል።

XS
SM
MD
LG